ነሐሴ 1/2017 ዓ.ም–ዞብል ፖስት ዜና!
ከህወሓት አፈንግጠው በወጡ ወታደራዊ አመራሮች እና ታጣቂዎች የተመሰረተው የትግራይ የሠላም ኃይሎች ቡድን በአፋር ክልል ዋና መቀመጫ ሰመራ ከተማ ቢሮ መክፈቱን ለዞብል ፖስት የደረሰው መረጃ ያሳያል።
ከዚህ ቀደም “የነፃ መሬት ታጣቂ” ይባል የነበረው ኃይል ራሱን “የትግራይ የሠላም ኃይሎች” ብሎ የቀየረ ሲሆን፣ አፋር ክልልን ጨምሮ በተለያዩ ቦታዎች ወታደራዊ ስልጠና እንደሚያደርግ ይታወቃል።
ታጣቂ ቡድኑ፣ በአፋር ክልል መጋሊ፣ አምባላጌ ቦራ ካምፕ በሚባሉ ቦታዎች የወታደራዊ ስልጠና የሚያደርግ ሲሆን፣ ታጣቂዎች የዋግህምራ እና ጠለምት አካባቢዎች በተደጋጋሚ መታየቸውንም ለመጽሔታችን የደረሰው መረጃ ያሳያል።
የትግራይ የሠላም ኃይሎች ከተመሰረተ በኋላ ከህወሓት ታጣቂዎች ጋር በተለያዩ ጊዜያት ውጊያ ያደረገ ሲሆን፣ ቡድኑ አቶ ጌታቸው ረዳ የሚመሩት ስምረት ፓርቲ ወታደራዊ ክንፍ ስለመሆኑ እና በዐቢይ አህመድ መንግሥት እንደሚደገፍ በርካታ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
የትግራይ ሠላማዊ ኃይሎች አመራር እንደሆኑ የሚነገርላቸው ጄኔራል ወዲ አሸብር በቅርቡ ወደ አፋር ሰመራ ተጉዘው ታጣቂ ቡድኑ የከፈተውን ቢሮ መጎብኘታቸው ተነግሯል።
ጄኔራሉ ከዚህም በተጨማሪ የታጣቂ ቡድኑ በርካታ ኃይል በሚገኝበት የአፋር ክልል መጋሊ ቀጠና ተገኝተው የቡድኑን የሎጅስቲክ ማዕከልና የሠራዊቱን ቁመና በአካል ተገኝተው ጎብኝተዋል ተብሏል።


